የካቲት 15፣2016 - የዝቋላ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ገዳምና ቅርሱን መንግስት እንዲታደጋቸው ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አሳሰበች
- sheger1021fm
- Feb 23, 2024
- 1 min read
የዝቋላ ደብረ ከዋከብት አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ገዳም፣ መናንያን እና ቅርሱን መንግስት እንዲታደጋቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አሳሰበች፡፡
ከትናንት በስትያ የገዳሙን መጋቢ ጨምሮ 4 አገልጋይ አባቶች በታጣቂዎች መገደላቸውን ከሃገረ ስብከቱ መረጃ ደርሶኛል ብላለች ቤተ ክርስቲያኗ፡፡
አገልጋዮቹ ባለፈው የካቲት 12 ‘’ኦነግ ሸኔ’’ በተባለው ታጣቂ ቡድን ከተወሰዱ በኋላ 4ቱ እንደተገደሉ አንድ አባት ደግሞ ቆስለው በገዳሙ እንደሚገኙ ከመነበረ ፓትርያርክ ጽ/ቤት የወጣው መግለጫ ያሳያል፡፡
በእለቱ በታጣቂ ቡድኑ የተገደሉት የገዳሙ መጋቢ አባተክለማሪያም አስራት፣ የገዳሙ ፀሀፊ አባ ኪዳነማርያም ጥላሁን፣ የገዳሙ የመፅሐፍ መምህርና ቀዳሽ አባ ገ/ማሪያም አበበ እና በአመክሮ የሚኖሩ መናኝ ኃ/ማርያም ወልደሰንበት ናቸው፡፡

ቆስለው በገዳሙ እንዳሉ የተነገሩት ደግሞ አባ ኪዳነማሪያም ገ/ሰንበት የተባሉ አባት ናቸው ተብሏል፡፡
ጥንታዊና ታሪካዊ ከሆኑ ገዳማት መካከል የሆነው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ገዳም ታጣቂዎች ለመግባት እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት መንገድ እንዲገደብም ቤተ ክርስቲያኒቱ ባወጣችው መግለጫ ጠይቃለች፡፡
መነኮሳቱን እና ቅርሱን የፌዴራልና የክልሉ የፀጥታ አካላት እንዲታደጓቸውም አሳስባለች፡፡
የኦሮሚያ ሰላምና ፀጥታ ቢሮም በጉዳዩ ላይ መግለጫ አውጥቷል፡፡
አራቱ የገዳሙ አባቶች በ’’ሸኔ’’ መገደላቸውን አረጋግጦ ድርጊቱ ማህበረሰቡን ያስደነገጠና ያስቆጣ መሆኑን ጠቅሷል፡፡
‘’በደረሰኝ ጥቆማ መሰረትም በታጣቂ ቡድኑ ላይ እርምጃ እየወሰድኩ ነው’’ ብሏል፡፡
የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ከክልሉ ፖሊስ ጋር እየወሰደ ስላለው እርምጃ ውጤቱን ለህዝብ ይፋ እንደሚያደርግም ቢሮው በመግለጫው ጠቅሷል፡፡
ትዕግስት ዘሪሁን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Yorumlar