የባህርማዶ ወሬዎች - ሐምሌ 9 2017
- sheger1021fm
- Jul 16
- 1 min read

ዩክሬይን
የዩክሬይኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴኒስ ሺማይሐል የስልጣን መልቀቂያ ደብዳቤ አስገቡ፡፡
ቀደምሲል የዩክሬይኑ ፕሬዘዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ ተቀዳሚ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው የቆዩትን ዩሊያ ሲቪሪዴንኮን ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ማጨታቸውን እወቁልኝ እንዳሉ ሬውተርስ ፅፏል፡፡
የሺማይሐልየስልጣን መልቀቂያ ደብዳቤ ማስገባት በዚህ ሳምንት በዩክሬይን መንግስት ውስጥ ይከናወናል የተባለው ሹም ሽር አካል ነው ተብሏል፡፡
የሹም ሽሩ ለአገሪቱ ፓርላማ ውሳኔ እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡
የመከላከያ ሚኒስትር ሆነው የቆዩት ሩስቴም ኡሜሮቭ በአሜሪካ የዩክሬይን አምባሳደር እንደሚደረጉ ተነግሯል፡፡
ዜሌንስኪ ለውጡ በእጅጉ አስፈላያችን ነው ማለታቸው ተሰምቷል፡፡

በሶሪያ መንግስት ሀይሎች ላይ ድብደባ የተፈፀመው የድሩዝ እምነት ተከታይ ማህበረሰቦች መኖሪያ ወደሆነችው ስዌይዳ ከተማ ለመዝለቅ በሞከሩበት ወቅት አንደሆነ የእስራኤል የጦር ሹሞች መናገራቸውን ቢቢሲ ፅፏል፡፡ የከተማዋ ድሩዝ ማህበረሰብ አባሎች ከበድዊን ጎሳዎች ጋር ሲጋጩ መሰንበታቸው በመረጃው ተጠቅሷል፡፡
የእስራኤል መንግስት የሶሪያ ጦር በድሩዞቹ ላይ ተደጋጋሚ ጥቃት እያደረሰ ነው ሲል ይከሳል፡፡ የሶሪያ መንግስት የታጠቁ ወታደሮቼን ወደ ስዌይዳ የላኩት በዚያ በተፋላሚ ወገኖቹ መካከል የተደረሰውን የተኩስ አቁም ለማስከበር አልሜ ነው በማለት ላይ ይገኛል፡፡ በእስራኤል ድብደባ በሶሪያ መንግስት ሀይሎች ላይ ስለደረሰው ጉዳት በዝርዝር የተጠቀሰ ነገር የለም፡፡

ኒውዮርክ
የተባበሩትመንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ለእስራኤል እና ፍልስጤማውያን ነባር ችግር ሁነኛው መፍትሄ የሁለት መንግስታት መሳ ለመሳ መኖር ነው አሉ፡፡
ጉዳዩ የሁለት መንግስታት መፍትሄ በሚል ለበርካታ አመታት ሲነሳ የቆየ መሆኑን አናዶሉ አስታውሷል፡፡
የሁለት መንግስታት መፍትሄ ፍልስጤማውያንም የነፃ አገር ባለቤቶች እንዲሆኑ የሚጠይቅ ሀሳብ ነው፡፡
ጉቴሬዝ በጋዛ የተኩስ አቁም ብቻ መደረሱ በቂ አይሆንም ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት የእስራኤል የፖለቲካ ሹሞች የሁለት መንግስታትን የመፍትሄ ሀሳብ ወደ ጎን እያሉት መምጣታቸው ይነገራል፡፡
እስራኤል በአሁኑ ወቅት በጋዛ የምታካሂደውን የጦር ዘመቻ እያሰፋችው ነው ይባላል፡፡

ኮንጎ ኪንሻሳ
በኮንጎ ኪንሻሳ ከተከሰተ የቆየው የኮሌራ ወረርሽኝ በጣሙን እየተስፋፋ ነው ተባለ፡፡
ወረርሽኙ ከመንፈቅ በላይ ማስቆጠሩን ዘ ኢስት አፍሪካን ፅፏል፡፡
በአሁኑ ወቅትም ኮሌራ አገሪቱ ካሏት 37 ግዛቶች በ17ቱ በጣሙን እየተዛመተ መሆኑን የጤና ሚኒስትሩ ሮጀር ካምባ ተናግረዋል፡፡
ወረርሽኙ አሁን አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል ብለዋል ሚኒስትሩ፡፡
ትሾፖ የተሰኘው ግዛት ደግሞ የኮሌራ ወረረሽኙ በእጅጉ የበረታበት እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡
በበሽታው ከሚያዙት መካከል የ3 በመቶዎቹ ሕይወት እያለፈ መሆኑን በመረጃው ተጠቅሷል፡፡
የጎርፍ መደጋገም እና የንጹህ ውሃ እጦት ወረርሽኙን ካባባሱ ምክንያቶች መካከል ናቸው ተብሏል፡፡
የኔነህ ከበደ












Comments