ወጣቶችና ታዳጊዎችን ከሱሰኝነት ለመጠበቅ የሚከወኑ ስራዎች ቢኖሩም ከማገገሚያ ከወጡ በኋላ መልሰው ችግር ውስጥ የሚገቡት ቁጥር ከፍተኛ ነው ተባለ፡፡
- Jun 9
- 2 min read
ሰኔ 2/2018
በኢትዮጵያ ወጣቶችና ታዳጊዎችን ከሱሰኝነት ችግር ለመጠበቅ የሚከወኑ ስራዎች ቢኖሩም ከማገገሚያ ከወጡ በኋላ መልሰው ችግር ውስጥ የሚገቡት ቁጥር ከፍተኛ ነው ተባለ፡፡
በተለይ በትምህርት ቤቶች አካባቢ ታዳጊዎችን ለሱስ የሚያጋልጡ ተቋማት አሁን መታየት ችግሩን ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ እንዳደረገው ተነግሯል፡፡

አንድ ሰው የሱሰኝነት ችግር ገጥሞት የማገገሚያ ህክምና አድርጎ ወደ ቀደመ ህይወቱ ለመመለስ ብዙ ጊዜ ወስዶ ቢሰራበትም ከዚህ ችግር ወጥተው መልሰው እዛው የሚገኙ ታዳጊዎች ቁጥር ከፍተኛ መሆኑን የሚናገሩት መቋሚያ የተባለ የማህበረሰብ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር እንዲሁም የሱስ ማገገሚያ ህክምና ላይ የሚሰሩት አቶ ኤልያስ ከላዩ ናቸው፡፡
ሱስን በማከም ሂደት ውስጥ ሲሰሩ መቆየታቸውን የሚናገሩት አቶ ኤሊያስ በማገገም ሂደት ህክምና ተደርጐላቸው ከሱስ ከወጡ በኋላ ወደ ችግሩ የሚመለሱ አሉ፡፡
በኢትዮጵያ ከሱስ ህክምና ጋር በተያያዘ ብዙ ተቋማት አለመስፋፋታቸው አንዱ ችግር መሆኑን የሚጠቅሱት አቶ ኤልያስ ወጣቶቹ ከችግሩ ወጥተው ሙሉ ለሙሉ ወደ ትምህርታቸውና የቀደመ ህይወታቸው እንዲመለሱ መስራቱ ቀድሞ ከመከላከሉ እኩል ሊሰራበት ይገባል ይላሉ፡፡
ታዳጊዎችንና ወጣቶችን ለሱስ እንዳይጋለጡ ከሚሰራው ስራ እኩል ችግር ውስጥ የገቡ ሰዎች ከችግሩ ለማውጣት ጥረት ማድረግ በቂ ድጋፍ በተለይ በትምህርት ተቋማት ዙሪያ መስራት ለችግሩ መፍትሄ ለመስጠት ዋነኛ ስራ መሆን አለበት ተብሏል፡፡
በትምህርት ቤቶች ዙሪያ የሚታዩና ታዳጊዎችን ለችግር ከሚደረጉ ተቋማት ቁጥጥር አኳያ ምን እየሰራችሁ ነው ስንል የአዲስ አበባ ምግብና መድሃኒት ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ሙሉእመቤት ታደሰ ጠይቀናል፡፡

ትምህርት ተቋማትን ከዚህ ችግር ለጠበቅ መመሪያ ተሰናድቶ ስራ ላይ መሆኑን ነገር ግን መመሪያውን ሙሉ ለሙሉ ለማስፈጸም የሚገጥሙ ችግሮች እንዳሉና በተለይ በዘመናዊ መልኩ ተሰርተው የሚቀርቡ የኤሌክትሮኒክስ የትምባሆ ዓይነቶች በማይታይ መልኩ ወደ ትምህርት ተቋማት እንደሚገቡና ለታዳጊዎች ችግር እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያ ከሱስ ማገገሚያ ማዕከላት ህክምናቸውን አጠናቀው ከሚወጡት ውስጥ እስከ 73 በመቶ የሚሆኑት በሶስት ወራት ጊዜ መልሰው ወደ ችግሩ እንደሚገቡ ጥናት ያሳያል፡፡
ለሱስ አጋላጭ የሚያደርጉ ነገሮችን መልሶ በቀላሉ ማግኘት መቻል፣ በወጣቶች ላይ ያወቻዎቻቸው ተጽዕኖ እንዲሁም በቂ የስነ ልቦና ድጋፍ በተከታታይ አለማግኘት ለዚህ ምክንያቶች እንደሆኑ ተጠቅሷል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ….
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i





Comments