ከጎርጎርሳውያኑ ከ2024 ጀምሮ ኢትዮጵያ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ከአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች ተብሏል።
- Mar 5
- 2 min read
የካቲት 26/2018
ከጎርጎርሳውያኑ ከ2024 ጀምሮ ኢትዮጵያ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ከአፍሪካ ሁለተኛ ፤ ከምስራቅ አፍሪካ ደግሞ አንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች ተብሏል።
በቀጣይ ወር በአዲስ አበባ በሚዘጋጀው የኢንቨስትመንት ፎረም ላይ ብቻ ከ2.4 ቢሊየን ዶላር በላይ ግምት ያለው የኢንቨስትመንት ስምምነት ይፈረማል ተብሎ እንደሚጠበቅም ተነግሯል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እና የገንዘብ ሚኒስቴር ፎረሙን አስመልክተው ትናንት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
ኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት እና ሌሎች ዘርፎችን የሚደግፉ ከ123 በላይ አዳዲስ ህጎችን ባለፉት ሰባት ዓመታት አውጥታለች ተብሏል።
ማሻሻያ የተደረገባቸው ህጎች ከተጨመሩበት ደግሞ ቁጥሩ ከ198 እንደሚልቅ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽነር ዶክተር ዘለቀ ተመስገን ተናግረዋል።

ከወጡ ህጎች አንዳንዶቹ ለውጪ ባለሃብቶች ዝግ የነበሩ ዘርፎች እንዲከፈቱ ያስቻሉ ናቸው ብለዋል።
እነዚህን ጨምሮ በመንግስት በከል የተወሰዱ የተለያዩ እርምጃዎች ኢትዮጵያን በተሻለ መልኩ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እያደረጓት እንደሚገኙ ጠቅስዋል።
ከጎርጎርሳውያኑ ከ2024 ጀምሮ ኢትዮጵያ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ከአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች ነው ያሉት።
በኢትዮጵያ ሲሰሩ የቆዩ እና በተለያየ ምክንያት ለቀው የሄዱ ባለሃብቶች እንዳሉ በተለያየ መንገድ ሲነገር ይሰማል ፤ ይህ ከኮሚሽኑ መረጃ ጋር እንዴት ይጣጣማል? በሚል የተጠየቁት ኮሚሽነሩ ተከታዩን ምላሽ ሰጥተዋል።
ኢትዮጵያ አራተኛውን የኢንቨስትመንት ፎረም መጋቢት 17 እና 18 /2018 በአዲስ አበባ እንደምታሰተናግድም ተነግሯል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ፤ የገንዘብ ሚኒስቴር እና አጋር አካላት በትብብር የሚያዘጋጁት ፎረም እንደሆነ ነው የሰማነው።
በፎረሙ ላይ ከ2.4 ቢሊየን ዶላር በላይ ግምት ያለው የኢንቨስትመንት ስምምነት ይፈረማል ተብሎ እንደሚጠበቅ ኮሚሽነር ዘለቀ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡
ለኢንቨስትመንት ፍሰቱ ፈተና የሆኑ አንዳንድ የፀጥታ ችግሮች በተለያዩ አካባቢው እንዳሉ ይታወቃል ያሉት፤ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው መንግስት እነዚህም ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በፎረሙ ላይ ከ800 በላይ አለም አቀፍ ባለሃብቶች ፤ የንግድ መሪዎች ፤ ፖሊሲ አውጪዎች የልማት አጋሮች ይታደማሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተነግሯል፡፡
ንጋቱ ረጋሣ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7





Comments