በአካባቢ ጥበቃ እና እንክብካቤ ላይ የሚሰራው 'ግሪን ዌቭ አልያንስ' ሀገር በቀል ግብረ ሰናይ ድርጅት ''የኢትዮጵያን የተራቆቱ አካባቢዎች አረንጓዴ የማልበስ ስራዬን እገፋበታለሁ'' አለ።
ድርጅቱ በየዓመቱ አርቲስቶችን፣ ጋዜጠኞችን እና ሌሎች ታዋቂ ሰዎችን እያስተባበር በተለያዩ አካቢቢዎች ችግኝ እያስተከለ ይገኛል።
ዘንድሮም ለ4ኛ ተከታታይ ዓመት ይህንኑ ፕሮግራም ከሞጆ ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር አካሄዷል።
በዚህም በእለቱ 10,000 ችግኞች መተከላቸው ተነግሯል።
የግሪን ዌቭ አልያንስ ድርጅት መስራች እና ዋና ስራ አስኪያጅ ሚኪ ነጋሳ፤ ድርጅታቸው ከሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር ላለፉት ሶስት ዓመታት የኪነ-ጥበብ ባለሞያዎች፣ አትሌቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ባለሀብቶች፣ አባ ገዳዎች እና የማኀበራዊ ሚዲያ አንቂዎች የሚሳተፉበት የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር ማዘጋጀቱን አስታውሰዋል።
የዘንድሮውን ጨምሮ ለአራቱ ዙር አረንጓዴ አሻራ መሳካት አስተዋፆ አድርገዋል የተባሉ የኪነ ጥበብ ሰዎች እና ጋዜጠኞች እውቅና ተሰጥቷቸዋል።
አርቲስት ችሮታው ከልካይ፣ ተዋናይ እና ጋዜጠኛ ተፈሪ ዓለሙ፣ ኮሜዲያን ደረጀ ሀይሌ፣ ጋዜጠኞቹ ጌጡ ተመስገን እና ፍሬው አበበ እውቅና ከተሰጣቸው መካከል ናቸው።
የሞጆ ከተማ ከንቲባ ጋዛል ሃሹ፣ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ዮናስ አያሌው፣ የባህል ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ነፊሳ አልማሃድ፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሀገር ሽማግሌዎች በዝግጅቱ ላይ ተገኝተዋል።
ንጋቱ ሙሉ
Comments