ነሐሴ 25፣2016 - በአዲስ አበባ ባጃጅ ለማሽከርከር የአዲስ አበባ ከተማ የነዋሪነት መታወቂያ መያዝ ያስፈልጋል ተባለ
- sheger1021fm
- Aug 31, 2024
- 1 min read
በአዲስ አበባ ባጃጅ ለማሽከርከር የአዲስ አበባ ከተማ የነዋሪነት መታወቂያ መያዝ ያስፈልጋል ተባለ።
ከዚህ በተጨማሪም የአዲስ አበባ የሠሌዳ ቁጥር እንዲሁም በማህበር መደራጀት ያስፈልጋል ሲል የከተማዋ ትራንስፖርት ቢሮ አስረድቷል።
በአዲስ አበባ ከተማ የባለሶስትና አራት እግር ተሽከርካሪ ወይም #ባጃጅ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች የአሰራር ፣የአጀረጃጀት፣ የአገልግሎት አሰጣጥና የዲሲፒሊን ቁጥጥር አፈጻጸም መመሪያ ላይ ውይይት መካሄዱ ተሰምቷል።
በአፈፃፀም መመሪያው የባለ ሶስትና አራት እግር ተሽከርካሪ ወይም ባጃጅ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ካሁን ቀደም ሲያጋጥሙ የነበሩ የሕግ ጥሰቶችንና የደንብ መተላለፎችን ለመከላከል ሲባል አገልግሎት ሰጪዎቹ የአዲስ አበባ ከተማ #የነዋሪነት_መታወቂያ ፣ የአዲስ አበባ የሠሌዳ ቁጥር እንዲሁም በማህበር መደራጀት እንደሚኖርባቸው ተነግሯል ።

በአዲስ አበባ፣ የከተማ አስተዳደሩን ታርጋ ለጥፈውና የአዲስ አበባ መታወቂያ ይዘው ከሚሰሩት ይልቅ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ አሽከርካሪዎች መበራከት የፀጥታ ችግር ሆነው ቆይተዋል ተብሏል።
ይህ ደግሞ በተለይም በወንጀል ድርጊት ላይ ተሳትፈው በሚገኙ አሽከርካሪዎች ላይ ህጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ጭምር አዳጋች እንደነበር ተጠቅሷል።
የባጃጅ ትራንስፖርት የከተማዋን ዘመናዊ እሳቤ የሚመጥን ስላልሆነ በሂደት መሉ በሙሉ አገልግሎቱ ይቋረጣል ተብሏል።
እስከዚያው ግን የባለሶስት እግር አሽከርካሪዎች የአዲስ አበባ መታወቂያ፣ ታርጋና በማህበር መደራጀት ይኖርባቸዋል ተብሏል።
ነገር ግን አሁን ላይ በተለይም በጋራ መኖሪያ ቤቶች አካባቢ ሰፊ የባጃጅ ትራንስፖርት አገልግሎ ፍላጎት በመኖሩ በነዚህ አካባቢ ያለው ፍላጎት በሌላ አማራጮች እስኪተካ ድረስ አገልግሎቱ ይቀጥላል ብሏል።
ንጋቱ ሙሉ
Comments