የስኳር መድሃኒት ጠፍቷል በሚል እየተሰራጨ ያለው መረጃ ሃሰት ነው በቂ የስኳር መድሃኒት አለ ሲል የኢዮጵያ መድሃኒት አቅራቢ አገልግሎት ተናገረ፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ማህበራዊ ሚዲያን እንዲሁም ሌላውን መንገድ በመጠቀም የስኳር በሽታን ለመቆጣጠር የሚረዱ መድሃኒቶች ጠፍተዋል፤ ገበያው ላይ የሉም በሚል ሃሰተኛ መረጃዎች እየተሰራጩ ነው የሚለው አገልግሎቱ፣ በመደበኛ በጀት የሚገዙ መድሃኒቶች በመሆናቸው ለቀጣዩ 8 ወራት የሚሆን ክምች አለ ብሏል፡፡
በኢትዮጵያ መድሃኒት አቅራቢ አገልግሎት የህዝብ ግንኙነት እና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክተሩ አቶ አወል ሃሰን 239 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው 5 አይነት የስኳር መድሃኒቶችን በመላው ኢትዮጵያ አሰራጫተናል፤ቀሪ 102 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው የስኳር መድሃኒቶች ለመጠባበቂያነት ይዘናል ብለዋል፡፡
ሆን ብለው የስኳር መድሃኒት እጥረት ፈጥረዋል ያሏቸውን ለመቆጣጠር ከኢትዮጵያ ምግብ መድሃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን ጋር በመሆን ምን እየሰራችሁ ነው ላልናቸው ሲመልሱ በቀጥታ መቆጣጠር ባንችልም ተለይተው እንዲታወቁ የአገልግሎት መስሪያ ቤቱን መለያ መድሃኒቶቹ ላይ እንለጥፋለን፤ ከተቆጣጣሪ መስሪያ ቤቱ ጋርም በጋራ እንሰራለን ብለዋል።
በቅርቡ ከተደረገው የዶላር የምንዛሪ ዋጋ መጨመር ጋር አያይዘው እጥረት አለ በሚል ሆን ብለው እጥረት በመፍጠር ለማትረፍ የሚፈልጉ የመድሃኒት መደብሮች እንዳሉ ሃላፊው ጠቁመዋል፡፡
ሃገሪቱ መድሃኒት፣ ማዳበሪያ እና ነዳጅን በድጎማ በመግዛት ስታቀር ቆይታለች፣ አሁንም ይኸው አሰራር ይቀጥላል፣ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ግዢው ላይ የሚያመጣው ለውጥ የለም ብለዋል ሃላፊው፡፡
የኢዮጵያ መድሃኒት አቅራቢ አገልግሎት ከ1ሺህ 20 በላይ ሁሉንም አይነት የህክምና መድሃኒቶችንና ግብአቶችን ከ5 ሺህ ለሚበልጡ የመንግስት የጤና ተቋማት እንደሚያቀርብ ከሃላፊው ሰምተናል፡፡
ምንታምር ፀጋው
Comments