ነሐሴ 16፣2016 - በደብረፅዮን ገ/ሚካኤል የሚመራው እና ያለምርጫ ቦርድ ፍቃድ ጉባኤ ያካሄደው ሕወሀት፤ ‘’ጊዜያዊ አስተዳደሩ በእኛ ተወካዮች መያዝ አለበት’’ አለ
- sheger1021fm
- Aug 22, 2024
- 1 min read
በደብረፅዮን ገ/ሚካኤል(ዶ/ር) የሚመራው እና ያለምርጫ ቦርድ ፍቃድ ጉባኤ ያካሄደው ሕወሀት፤ ‘’ጊዜያዊ አስተዳደሩ በእኛ ተወካዮች መያዝ አለበት’’ አለ፡፡
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው ‘’ከሰሞኑ ሕወሃት ያካሄደው ጉባኤ ሕገ-ወጥ መሆኑን ተናግረው የሚወሰኑ ውሳኔዎችም ተቀባይነት የላቸውም’’ ሲሉ ነግረውናል፡፡
ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል(ዶ/ር) ከሰሞኑ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ 14ኛ ጉባኤ ላይ ባልተሳተፉ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ቦታ አዳዲስ የማዕከላዊ የኮሚቴ አባላት መመረጣቸውን ተናግረዋል፡፡
የክልሉ ጊዜዊ አስተዳደር ፕሬዘዳንት ጌታቸው ረዳን ጨምሮ 14 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ከጉባኤው አስቀድሞ ራሳቸውን ማግለላቸው ይታወቃል፡፡
የሕወሃት ሊቀመንበር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) ‘’ጊዜያዊ አስተዳደሩ ላይ የህወሃት ሰዎች መመደብ አላባቸው’’ ብለዋል፡፡
‘’ሕወሃትን ወክለው የገቡ አሁን ሕወሃትን ስለማይወክሉ የሕወሃት ሰዎች በጊዜያዊ አስተዳደሩ ላይ መመደብ አለባቸው’’ ሲሉ ሊቀመንበሩ አስረድተዋል፡፡
አሁን በስልጣን ላይ ያለውን ‘’ግዴለም ሕወሓትን ወክል ካልተባለ በስተቀር ሕወሓትን አይወክልም’’ ብለዋል ደብረ ጽዮን ገ/ሚካኤል፡፡
ሕወሀት አሁን ‘’በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት የራሱ ያልሆኑ ሰዎችን አንስቶ የራሱን መመደብ ይችላል’’ ሲሉ በመግለጫው አንስተዋል፡፡
‘’ለዚህም ይህን ጊዜያዊ አስተዳደር ካቋቋመው አካላት ጋር ውይይይት ያስፈልጋል’’ ያሉት ሊቀመንበሩ ሕወሀት የነበሩ ‘’አሁን ሕወሓት ያልሆኑ አሉ በዚህም በስምምነቱ መሰረት ውይይት እንደሚያስፈልግ’’ አስረድተዋል፡፡
ራሳቸውን ከጉባኤው ያገለሉ አካላት ‘’በፊት ሕወሃት ነበሩ አሁን የራሳችን አቋም አለን ከእናንተ ጋር አንሄድም ብለዋል ቢፈልጉ የራሳቸውን ድርጅት ሊያቋቁም ይችላሉ የሕወሓትን ቦታ ግን መውሰድ አይችሉም’’ ሲሉ ዶክተር ደብረጽዮን አስረድተዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንዲሰጡን የጠየቅናቸው የክልሉ ጊዜያዊ ፕሬዘዳንት ጌታቸው ረዳ ‘’ሕወሃት ያካሄደው ጉባኤ ሕጋዊ እውቅና እንደሌለው ተናግረው ያሳለፋቸው ውሳኔዎችም ተቀባይነት የላቸውም’’ የሚል አጭር መለስ ሰተውናል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
Comments