ነሐሴ 14፣2016 - በመንገዶች ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ለጥገና የማወጣው ወጪ ከእጥፍ በላይ ጨምሮብኛል ሲል የመንገዶች አስተዳደር ተናገረ
- sheger1021fm
- Aug 20, 2024
- 1 min read
በመንገዶች ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ለጥገና የማወጣው ወጪ በአንድ ዓመት ውስጥ ብቻ ከእጥፍ በላይ ጨምሮብኛል ሲል የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ተናገረ፡፡
ከ2015 ዓመት በፊት ለመንገዶች መደበኛ እና ወቅታዊ ጥገና የሚወጣው ወጪ በአማካኝ ከ4 ቢሊዮን ብር ያልበለጠ ነበረ ያለው ተቋሙ በ2016 ዓ.ም ግን ወጪው ወደ 8 ቢሊዮን ብር መድረሱ ተናግሯል፡፡
‘’ይህ የሚያሳየው መንገዶቹ ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት ከፍተኛ መሆኑ ነው'' ሲሉ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር አለማየሁ አየለ(ዶ/ር) አስረድተዋል፡፡
''እየደረሰ ባለው ጉዳት የተነሳ ለ15 እና ለ20 ዓመታት እንዲያገለግሉ ታሳቢ ተደርገው የተገነቡ መንገዶች ብዙም አገልግሎት ሳይሰጡ እየተበላሹ ነው'' ብለውናል፡፡

''በተለይም ከባድ የጭነት ተሽከርካሪች ከተፈቀደላቸው የጭነት መጠን በላይ መጫናቸው ለመንገዶቹ መጎዳት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው ሲሉም ተናግረዋል'' ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፡፡
የኢትዮ ጂቡቲ መንገድ ከባድ የጭነት ተሽከርካሪዎች የሚመላለሱበት በመሆኑ ከሌሎች መንገዶች በበለጠ ሁኔታ ጉዳት የሚደርስበት እንደሆነ ተነግሯል።
አስተዳደሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ ባለፉት 25 ዓመታት 171,000 ኪ.ሜ መንገድ ተገንብቷል ብሏል፡፡
ለእነዚህ ግንባታ የወጣው ወጪም 525 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር በአሁን ወቅት፤ 30,440 ኪ.ሜ መንገድ እያስተዳደርኩ እገኛለሁ ብሏል፡፡
ማንያዘዋል ጌታሁን
Comments