ነሀሴ 20 2017 - በኢትዮጵያ የደም ህክምና የሚጠይቁ አንዳንድ የካንሰር ህመሞች በህክምናው ቱሪዝም ዘርፍ ብዙ የውጪ ምንዛሪ የሚያሳጣ ሆኖ ዘልቋል ተባለ
- sheger1021fm
- Aug 26
- 1 min read
የደም ህክምና የሚጠይቁ የካሰር ህመሞች እንደ አጥንት መቅኒ ንቅለ ተከላና ሌሎች ተመሳሳይ ህክምናዎች በሀገር ቤት ለመስጠትም ስራዎች መጀመራቸውን የኢትዮጵያ ደምና ህብረ ህዋስ ባንክ ተናግሯል፡፡
ህክምናዎቹ ሀገር ቤት ባለመኖራቸው ብዙዎች እንደሚቸገሩ እንዲሁም ህይወታቸውንም እንደሚያጡ የሚናገሩት የኢትዮጵያ ደምና ህብረህዋስ ባንክ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ሀብታሙ ታዬ በመጪው ዓመት ህክምናውን በሀገር ቤት ለመጀመሪያ የተጀመሩ ስራዎች አሉ ብለዋል፡፡
ከደም ጋር የተገናኙ አዳዲስ ህክምናዎች ለመጀመር በዚህ ዓመት ዝግጅት ሲደረግ ነበር የሚሉት አቶ ሀብታሙ በተለይ የካንሰር ታካሚዎች ህክምናው ሀገር ውስጥ ባለመኖሩ በጣም ሲቸገሩ ነበር ለዚህም ስራውን በሀገር ቤት ለመጀመር የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ተጀምረዋል ብለዋል፡፡

የህክምና አገልግሎቱን ለመጀመርም የባለሙያዎች ስልጠና እንዲሁም ግብዓቶችን የማሟላት ስራዎች ተጀምሯል የሚሉት አቶ ሀብታሙ በሚቀጥለው ዓመት አጋማሽ ላይ ወደ ስራ ለመግባትም ታስቧል ይላሉ፡፡
ባለሙያዎችን ወደ ውጭ በመላክ ስልጠናዎችን እንዲያገኙ እንዲሁም አገልግሎቱ ሲጀመር የሚያስፈልጉ ግብዓቶች በመኖራቸው እነዚህን ማሟላት ላይ እየተሰራ ነው ህክምናው በሀገር ውስጥ ቢጀመር በተለይ ከደም ካንሰር ጋር ተያይዘው የሚመጡ ህመሞችን ለማከም የመቅኔ ንቅለ ተከላ ህክምናው ትልቅ ተስፋ ነው ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ደምና ህብረ ህዋስ ባንክ የመቅኔ ህክምናውን ለመጀመርም ከበጎ ፈቃደኛች በሚገኝ ልገሳ ህክምናውን ለመጀመር ተሰናድቷል ተብሏል፡፡
አሁን ላይ በተቋሙ ሁለት ማሽኖች አሉ ሌሎችን በግዥ ለማስገባት ታስቧል የህክምና ሂደቱ በጣም ትልቅ ጥንቃቄ የሚፈልግ አይነት በመሆኑ እሱን በተመለከተ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ላይ በሚቀጥለው አመት ላይ ስራው እንዲጀምር በዝግጅት ላይ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት ያፀደቀችው የጤና አገልግሎት አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጅ የደም፣ ህዋስ፣ ህብረ ህዋስ፣ የአካል ክፍል ወይም የአካል ልገሳ እና የንቅለ ተከላ አገልግሎቶችን በበጎ ፈቃደኞች ለዚሁ አላማ ሲባል በተቋቋመ ማዕከል መለገስ እንዲቻል መፍቀዱ ለህክምና ስራው መጀመር አስተዋጽኦ አድርጓል ተብሏል፡፡
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments