ታህሳስ 30፣2016 - ነጻነት እና እኩልነት ፓርቲ ገዢው ብለጽግና ድርጅታዊ ስራውን ከመንግስት መዋቅር እንዲለይ ጠየቀ
- sheger1021fm
- Jan 9, 2024
- 1 min read
ነጻነት እና እኩልነት ፓርቲ ገዢው ፓርቲ ብለጽግና ድርጅታዊ ስራውን ከመንግስት መዋቅር እንዲለይ ጠየቀ፡፡
የፓርቲ አባል ያልሆኑ የመንግስት ሰራተኞች በብልጽግና ፓርቲ ስልጠና እንዲሳተፉ የሚደረግበት አሰራር እንዲቆም ነጻነት እና እኩልነት ፓርቲ ጠይቋል፡፡
በግብር ከፋዩ ገንዘብ የፓርቲ ስልጠና ማካሄድ ኢህገ መንግስታዊ በመሆኑ በአስቸኳይ እንዲቆም አሳስቧል፡፡
ችግሩ በአፋጣኝ መፍትሄ እንዲያገኝ ለሲቭል ሰርቪስ ኮሚሽን እና ሌሎች ጉዳዩ ለሚመለከያቸው አካላት ፓርቲው በደብዳቤ መጠየቁንም አስረድቷል።
ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ የመንግስት እና የፓርቲ መደበላለቅ በለውጡ ማግስት መጠነኛ መሻሻል አሳይቶ የነበረ መሆኑን አስታውሶ፣ ይሁን እንጂ ከ6ኛው ጠቅላላ ምርጫ ማግስት ጀምሮ ችግሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ መጥቷል ብሏል።
ከዚህ አኳያ ከቅርብ ወራት ጀምሮ ገዢው ፓርቲ እያካሄደ ባለው የአባላት ስልጠና፣ የፓርቲው አባል ያልሆኑ የፌዴራል እና የክልል የመንግስት ሰራተኞች (Public servants) የገዢውን ፓርቲ ድርጅታዊ ስልጠና እንዲወስዱ መደረጉ ህግ እና ስርአትን የጣሰ አካሄድ መሆኑን ፓርቲው ጠቅሷል፡፡
ለሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን እና ሌሎች የሚመለከታቸው የፌዴራል እና የክልል መንግስታት መስሪያ ቤቶች በላኩት ድብዳቤ አሳወቄለሁ ብሏል።

ከእዚሁ ጋር በተያያዘ ገዢው ፓርቲ የሚያካሄዳቸው ስልጠናዎች አበል፣ ትራንስፖርት፣ ሆቴል እና ሌሎች የስልጠና ወጪዎች በመንግስት በጀት መሸፈን ህገ ወጥ ተግባር መሆኑን ነጻነት እና እኩልነት ፓርቲ አስረድቷል፡፡
በመሆኑም የፓርቲ አባል ያልሆኑ የፌዴራል እና የክልል የመንግስት ሰራተኞች የገዢውን ፓርቲ ስልጠና እንዲወስዱ ማድረግም ሆነ የፓርቲ ስልጠናን በመንግስት በጀት ማካሄድ ህገ መንግስቱን እና አዋጃ ቁጥር 1162/2011 የሚቃረን በመሆኑ፣ የሚመለከታቸው አካላት ድርጊቱን ለማስቆም አስፈላጊውን እርምጃ እንዲወስዱ ፓርቲው ጠይቋል።
ንጋቱ ሙሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Website: https://www.shegerfm.com/
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments