ታህሳስ 16፣2017 - “ጥያቄዎቻችን ካልተመለሱልን ስራ የማቆም አድማና ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ እንገደዳለን” የኢትዮጵያ ሰራተኞች ማህበራት ኮንፌዴሬሽን አባል ማህበራት
- sheger1021fm
- Dec 25, 2024
- 1 min read
“ጥያቄዎቻችን ካልተመለሱልን ስራ የማቆም አድማና ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ እንገደዳለን” የኢትዮጵያ ሰራተኞች ማህበራት ኮንፌዴሬሽን አባል ማህበራት፡፡
“ይህንን ማድረግ ሳያስፈልግ መንግስት ምላሽ እንዲሰጥ ለማድረግ ጥረት እናደርጋለን፡፡” ኢሰማኮ
ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል በመንግስት እንዲወሰንና ከደመወዝ ላይ የሚቆረጠው #ከፍተኛ_ግብር እንዲቀንስ መንግስት በተደጋጋሚ ቢጠየቅም እስካሁን ምላሽ ባለመስጠቱ ከዚህ በኋላ ሰራተኞች ወደ ስራ ማቆም አድማና ወደ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያመሩ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌደሬሽን የኢትዮጵያን ሰራተኞች ይወክላሉ ከሚባሉት አባላቱ ጋር ባሳለፍነው ሳምንት አድርጎት በነበረው ጉባኤ ማጠቃለያ ላይ አባላቱ ባወጡት የአቋም መግለጫ፤ እስካሁን ስናነሳቸው የነበሩ ጥያቄዎቻችን በመንግስት ባለመመለሳቸው ከዚህ በኋላ የስራ ማቆም አድማ ለማድረግ እንዲሁም በሰላማዊ ሰልፍ ለመጠየቅ እንገደዳለን ማለታቸውን የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌደሬሽን የውጭና ህዝብ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ አቶ አያሌው አህመድ ነግረውናል፡፡
#የኢትዮጵያ_ሰራተኞች ወኪል ተደርገው የሚታዩት እነዚህ የኮንፌደሬሽኑ አባላት በአቋም መግለጫቸው ያሰፈሩት ወደ ተግባር ከማስገባታቸው በፊት ኮንፌደሬሽኑ ምን ለማድረግ አስቧል? ላልናቸው አቶ አያሌው ሲመልሱ፤ ሰራተኞቹ ወደዚህ ተግባር ከመግባታቸው በፊት የኮንፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ከመንግስት ምላሽ ለማግኘት የራሱን ጥረት ያደርጋል ብለውናል፡፡
በቋሚ ደመወዝ የሚተዳደሩ ሰራተኞች አሁን ያለውን የኑሮ ጫና መቋቋም እንዲችሉ የሚከፍሉት ግብር እንዲቀነስ ባሳለፍነው ጥቅምት ወር ጠቅላይ ሚኒስትሩን በደብዳቤ በድጋሚ መጠየቃቸውን ያስታወሱት ኃላፊው ደብዳቤው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መድረስ አለመድረሱን የምናረጋግጥ ይሆናል፤ ምላሻቸውንም እንጠይቃለን ብለዋል፡፡
ከዚህ በኋላ በጉዳዩ ዙሪያ በኮንፌደሬሽኑ መንግስትን በተለያዩ ደረጃዎች በድጋሚ በመጠየቅ ምላሽ የሚያገኝ ከሆነ በጉባኤው የተቀመጠውን ማድረግ ማለትም ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግም ይሁን የስራ ማቆም አድማ ማድረግ ሳያስፈልግ ችግሩ ይፈታል የሚል እምነት እንዳላቸው የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌደሬሽን የውጭና ህዝብ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ አቶ አያሌው አህመድ ነግረውናል፡፡
ኮንፌደሬሽኑ ከ2,300 በላይ ተቋማትን በስሩ የያዘ ነው፡፡
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ… https://tinyurl.com/5xu9mdpj
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Website: https://shorturl.at/yCz7q
📌 YouTube: https://t.ly/9uH-g
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments