ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የፋይናንስ ተቋማት ዳታን ወይም መረጃን ተንትኖ ውሳኔ መስጠት ላይ የእውቀት ክፍተት አለባቸው ተባለ፡፡
አሁንም ድረስ የፋይናንስ ዘርፉ ውሳኔዎችን እየሰጠ ያለው በባለሙያዎችእገዛ ብቻ ነው ተብሏል፡፡
ይህንን ክፍተት ለመሙላት ኤመራልድ ኢንተርናሽናል ኮሌጅና የካፒታል ፋይናንስ ልህቀት ማዕከል በመተባበር ባለሙያ ለማሰለልጠን ተዘጋጅተዋል፡፡
የካፒታል ፋይናንስ ልህቀት ማዕከል የስልጠናና ልማት ዳይሬክተር ሃብታሙ አበባው(ዶ/ር) ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የፋይናንስ ዘርፍ ቴክኖሎጂን ተንተርሶ ዳታ መተንተን ላይ የእውቀት ክፍተት መኖሩን ነግረውናል፡፡
ማዕከሉ ከተቋቋመ 2 ዓመት ሆኖታል፡፡ በዚህ ወቅት ከለተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት ከቴክኖሎጂና ተያያዥ ጉዳዮች ስልጠና ሲሰጥ እንደነበር ያስረዳሉ፡፡
አሁን ተወዳዳሪ ለመሆን የቴክኖሎጂ ዳታ ወይም መረጃ አጠቃቀምን መረዳት ያስፈልጋል ያሉት ዶክተር ሃብታሙ ከኤመራልድ ጋር በመሆን የሚሰጠው ስልጠና ይህንን ክፍተት እንዲሞላ በማሰብ ነው ብለዋል፡፡
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚንስትር ድኤታ ዶክተር ባይሳ በዳዳ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የፋይናንስ ዘርፍ ለማሳደግና ትክክለኛ ውሳኔ ለመወሰን አሁን በዳታ ላይ መመስረት ግዴታ ነው በማለት ጠቅሰዋል፡፡
የዳታ ሳይንስ መምህር የሆኑት ስንታየሁ ዲፓስ(ዶ/ር) ኢትዮጵያ ውስጥ በቴክኖሎጂው ዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎች እውቅና ሲያገኙ አለማቀፍ ሊሆን ይገባል ብለዋል፡፡
ወደ ሀገር ቤት እየገቡ ያሉ አርተፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂም ሆነ ሌሎች ቴክኖሎጂዎች የኢትዮጵያን ችግር መፍታት አይችሉም፤ ምክንያቱ ደግሞ ቴክኖሎጂዎቹ ሲሰሩ ኢትዮጵያን መሰረት አድርገው ስላልሆነ ነው ይላሉ፡፡
በመሆኑም የራሳችንን ቴክኖሎጂ ማልማት የተሻለ መፍትኤ በመሆኑ በሙያው ብቁ ሰዎችን ማፍራት ለነገዬ መባል የሌለበት ስራ መሆኑም ተነግሯል፡፡
በረከት አካሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 YouTube: https://t.ly/9uH-g
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments