በንግድ ስራ መሰማራት ለሚፈልጉ ሰዎች ምቹ ሁኔታዎች እንዲኖሩ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ተናገረ።
- Feb 26
- 2 min read
የካቲት 19/2018
በንግድ ስራ መሰማራት ለሚፈልጉ ሰዎች ምቹ ሁኔታዎች እንዲኖሩ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ተናገረ።
በህጋዊ መንገድ በስራው ለመሳተፍ የሚገጥሙ ችግሮች ሰዎችን ወደ ህገ ወጥ መንገድ እየገፉ ነው ተብሏል።
በኢትዮጵያ ህጋዊ ያልሆነ ንግድ ከመቀነስ ይልቅ እየተባባሰ መምጣቱን ከሠሞኑ የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ባዘጋጀው አንድ ውይይት ላይ ሲነገር ሠምተናል።
ለዚህ እንደ ማሳያ የሚጠቀሰው በኮንትሮባንድ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባ መድሃኒት ነው።
መድሃኒት አምስት በመቶ እንኳን የማይሞላ በጣም አነስተኛ ቀረጥ እና ታክስ ተከፍሎባቸው ወደ ሀገር ውስጥ ከሚገቡ ምርቶች አንዱ እንደሆነ ፤ የኢትዮጵያ ጉሙሩክ ኮሚሽን የህግ ተገዥነት ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር አቶ እዘዘው ጫኔ ይናገራሉ።
እንዲያም ሆኖ በከፍተኛ መጠን በኮንትሮባንድ ወደ ሀገር ውስጥ ከሚገቡት አንዱ መድሃኒት ነው ብለዋል።
ሁኔታው ህገ ወጥ የመድሃኒት ንግድ ቀረጥ እና ታክስ ለመክፈል ባለ መፈለግ ብቻ ተስፋፋ ማለት እንደማያስችል አክለዋል።
ህጋዊ በሆነ መንገድ በስራው መሰማራት ለሚፈልጉ ሰዎች ነገሮች ምን ያህል ምቹ ናቸው? የወጡ ህጎችስ ተናበዋል ወይ? ብሎ መጠየቅ አስፈላጊ እንደሆነ ተናግረዋል።
እኛም ሰዎች ህጋዊ በሆነ መንገድ ንግድ እንዲያካሂዱ ሥርዓቱ ምን ያህል ምቹ ነው ስንል ለንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ጥያቄ አቅርበናል።
በሚኒስቴሩ የሀገር ውስጥ ንግድ መሪ ስራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ ሊቁ በነበሩ በህጋዊ መንገድ ለመስራት አሁን ላይ ብዙ ውጣ ውረድ የለም ሲሉ መልሰዋል።
ሰዎች በህጋዊ መንገድ እንዲሰሩ ምቹ ህጎች ቢኖሩም ህጉን የማያከብሩ ሰዎች ካሉ ነገሮች አስቸጋሪ መሆናቸው አይቀርም።
ባለሞዎች የወጡ ህጎችን አክብረው ጠንካራ በሆነ መንገድ ማስፈጸም አለባቸው የሚለው የእኛም አቋም ነው የሚሉት አቶ ሊቁ ፤ ይህን በማያደርጉት ላይ ጠንከር ያለው እርምጃ ወስደናል ሲሉ ነግረውናል።
ሰዎችም በህጋዊ መንገድ ለመስራት ችግር ሲገጥማቸው ህጋዊ ያልሆነውን መንገድ መምረጥ የለባቸውም የሚሉት አቶ ሊቁ፤ መብታቸውን በማስከበር የመንግስትን ጥረት ማገዝ አለባቸው ብለዋል።
በኮንትሮባንድ ከኢትዮጵያ የሚወጡ ሸቀጦች ዋጋ ግምት በ5 ዓመታት ውስጥ ብቻ ከ 1 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወደ 8 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ማደጉ ተጠቅሷል።
በ2011 ዓ.ም 340 ሚሊየን ብር የነበረው በኮንትሮባንድ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ሸቀጦች ዋጋ ግምት በ2015 ዓ.ም ወደ 2 ነጥብ 74 ቢሊየን ብር ከፍ ማለቱ ተነግሯል።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ….
ንጋቱ ረጋሣ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7





Comments