በመጪው ዓመት ከአዲስ አበባ ከተማ ግብር ከፋዮች 380 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ውጥን መያዙን የከተማዋ ገቢዎች ቢሮ ተናገረ።
- Aug 5
- 1 min read
ሐምሌ 29 2018
በመጪው ዓመት ከአዲስ አበባ ከተማ ግብር ከፋዮች 380 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ውጥን መያዙን የከተማዋ ገቢዎች ቢሮ ተናገረ።
በ2019 በጀት ዓመት በአዲስ አበባ ከተማ ደረጃ በአጠቃላይ 502.2 ቢሊዮን ብር ይሰበሰባል የተባለ ሲሆን ከዚህም ውስጥ የገቢዎች ቢሮ ድርሻ 380 ቢሊዮን ብር መሆኑን ቢሮው ዛሬ በሰጠው መግለጫ ተናግሯል።
የከተማ አስተዳደሩም ከሚሰበሰበጡ ግብር 72 በመቶውን ከተማዋን ለማልማት እንደሚያውለው መግለጫውን የሰጡት የገቢዎች ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ አስረድተዋል።
በከተማዋ በንግድ ትርፍ፣ በኪራይና በሜትር ትራንስፖርት ዘርፍ የተሰማሩ 456 ሺህ የደረጃ ለ - ግብር ክፋዮች አሉኝ ያለው ቢሮው፤ በተሻሻለው የገቢ ግብር አዋጅ መሰረት የግብር ግዴታቸውን ከሐምሌ 1 እስከ ሐምሌ 30/2018 ዓ.ም መክፈል እንዳለባቸውም አስታውሷል።
ከደረጃ ''ለ'' ግብር ከፋዮች በዘንድሮ በጀት ዓመት ቢሮው 9.2 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ውጥን ይዟል ያሉት አቶ ሰውነት፤ እስካሁን መረጃው ለተሟላላቸው ግብር ክፋዮች የግብር ውሳኔ በስልካቸው በመልዕክት (በቴክስት) እንዲደርሳቸው ተደርጓል፤ በዚህም አብዛኛው ግብር ክፋይ በወቅቱ ግብሩን ከፍሏል፤ ቀሪዎቹም እየከፈሉ ይገኛሉ ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ስለሆነም እስከ ሀምሌ 25 ድረስ ዓመታዊ ግብራችሁን እንድትከፍሉ መልዕክት በስልካችሁ የተላከላችሁ ግብር ከፋዮች በሙሉ እስከ ሀምሌ 30/2018 ዓ.ም ብቻ ያለ ቅጣት መክፈል እንደሚችሉ አሳውቀዋል።
ይሁንና በተለያዩ ምክንያቶች ቴክስት ያልደረሳችሁ ግብር ከፋዮች እንዲሁም ከሀምሌ 25 በኋላ መልዕክት የተላከላችሁ ግብር ክፋዮች ወደ ቅጣት የማትግቡ በመሆኑ ቴክስት ከተላከላችሁ ጊዜ ጀምሮ እስከ ነሀሴ 20/2018 ዓ.ም ባሉት ቀናት ውስጥ አመታዊ ግብራችሁን መክፈል ትችላላችሁ ብለዋል።
እስካሁን መልዕክት ያልደረሳችሁ ደግሞ የቴክስት መልዕክት እስከሚላክላችሁ ድረስ በትዕግስት እንድትጠባበቁን ሲሉ ሀላፊው አሳስበዋል።
ምንታምር ጸጋው
_edited.jpg)




Comments