ሰኔ 27 2017 - ''የመውጪ ፈተና አሰጣጥ ቴክኒካል ኮሚቴ ውስጥ፤ ከ2016 ጀምሮ እየተወከልን አይደለም'' የግል ከፍተኛ ትምህርትና ቴክኒክና ሞያ ተቋማት ማህበር
- sheger1021fm
- 5 days ago
- 1 min read
የመውጪ ፈተና አሰጣጥ ቴክኒካል ኮሚቴ ውስጥ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋም፤ ከ2016 ጀምሮ እየተወከልን አይደለም ሲል የግል ከፍተኛ ትምህርትና ቴክኒክና ሞያ ተቋማት ማህበር ተናገረ፡፡
ከሶስት ዓመታት በፊት የወጣው የከፍተኛ ትምህርት የመውጫ ፈተና ማስፈፀሚያ መመሪያ የፈተና አሰጣጥ ቴክኒካል ኮሚቴ ውስጥ ከግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማህበር 2 ተወካዮች አባል እንዲሆኑ ይፈቅዳል፡፡
የግል ከፍተኛ ትምህርትና ቴክኒክና ሞያ ተቋማት ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተፈራ ገበየሁ፤ ይህ መመሪያ ከባለፈው 2016 ዓመት ጀምሮ እየተተገበረ አይደለም ይላሉ፡፡
የትምህርት ሚኒስቴር ለግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የፈተና ውጤት መረጃዎችን በሚገባ እየሰጠ ነው ነገር ግን ለማህበሩ በሚገባ ተንትኖ አይነግረንም ሲሉ አቶ ተፈራ ገበየሁ አስረድተዋል፡፡

የመውጪ ፈተና እንደተጀመረ አካባቢ በግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ዝቅተኛ ውጤት ያስመዘግቡ የነበረው በወቅቱ ወደእነዚህ ተቋማት ለመማር የሚገባው ተማሪ ውጤትያነሰ ስለነበር ነው ተብሏል፡፡
ከ2014 ወዲህ በተጀመረው አዲሱ አሰራር ግን ይህ ችግር ተቀርፏል፤ ምክንያቱም ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግባት የሚችለው ተማሪ 50 ከመቶና ከዚያ በላይ ውጤት ማምጣት ሲችል ብቻ በመሆኑ ነው ሲሉ ያስረዳሉ፡፡
በዩኒቨርሲቲ መውጫ ፈተና የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል የሚሉት አቶ ተፈራ ገበየሁ በጋራ ከሰራንና ከተቀራረብን በዘርፉ የሚታዩ ችግሮች በቀላሉ መፍታት እንችላለን በማለት ተናግረዋል፡፡
የመውጪ ፈተና አሰጣጥ ቴክኒካል ኮሚቴ ዙሪያ በተነሳው ቅሬታ፤ የትምህርት ሚኒስቴር የስራ ኃላፊዎችን ጠይቀን የነበረ ሲሆን ምላሽ ማግኘት ግን አልቻልንም፡፡
የመውጪ ፈተና አሰጣጥ ቴክኒካል ኮሚቴ የፈተና አሰጣጥ ሂደቱ በተገቢው መንገድ እየተካሄደ መሆኑን በሚገባ እንዲከታተልና እንዲያስፈጽም መመሪያው ያዛል፡፡
በረከት አካሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments