ሰኔ 27 2017 አዋሽ ኢንሹራንስ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ4.5 ቢሊዮን ብር በላይ አረቦን ሰበሰብኩ አለ።
- sheger1021fm
- 4 days ago
- 1 min read
አዋሽ ኢንሹራንስ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ4.5 ቢሊዮን ብር በላይ አረቦን ሰበሰብኩ አለ።
ይህም ከግል ኢንሹራንስ ኩባንያዎች ሁሉ በሰፊ ልዩነት የመሪነት ስፍራውን ይዤበታለሁ ብሏል፡፡
ኩባንያዉ በጠቅላላ መድን ሥራ (General Insurance) ከ3.74 ቢሊዮን ብር በላይ አረቦን ገቢ መሰብሰቡን የተናገረ ሲሆን የ44 በመቶ የሽያጭ ገቢ እድገት አስመዝግቧል ተብሏል፡፡
በሕይወትና ጤና መድን (Life Assurance) ስራ ዘርፍም ደግሞ ከ656 ሚሊዮን ብር በላይ አረቦን ገቢ በማግኘት የ48 በመቶ ዕድገት ማስመዝገቡን አስረድቷል።
በሸሪዓ መርሆች የሚተዳደር ሠላም ተካፉል በተሰኘው ኢንሹራንስ አገልግሎቱ ደግሞ ከ150 ሚልዮን ብር በላይ አረቦን በመሰብሰብ በዘርፉ የ120 በመቶ ዕድገት ማስመዝገብ መቻሉን የተናገረው አዋሽ ኢንሹራንስ በአጠቃላይ በሶስቱም የስራ ዘርፎች ከ4.5 ቢሊዮን ብር በላይ አረቦን ሰብስቤያለሁ ሲል ለሸገር በላከው መግለጫ አስረድቷል።

በዚህም ከአምና ተመሳሳይ ወቅት ሲነፃፀር 46 በመቶ ማሳየቱ ተጠቅሷል።
በሌላ በኩል ኩባንያው በአጠቃላይ የኢንሹራንስ ዘርፍ (General Insurance) የካሣ ክፍያ መጠን ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ የደረሰ መሆኑ የተነገረ ሲሆን ከዚህ አጠቃላይ የካሳ መጠን ውስጥ የተሽከርካሪዎች ብቻውን ከ930 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱ ተነግሯል፡፡
ኩባንያው 3 አገናኝ ቢሮዎችን ጨምሮ የአገልግሎት መስጫ ቢሮዎችን በአጠቃላይ 71 መድረሳቸውን ሰምተናል፡፡
አዋሽ ኢንሹራንስ አ.ማ የግብርና ዘርፍ ከተፈጥሮ አደጋና ከአየር ንብረት መዛባት የሚታደገዉን የሰብል መድን አገልግሎት በዘንድሮው አመት መስጠት መጀመሩንም አስረድቷል፡፡
የኩባንያው የተከፈለ ካፒታል 2.6 ቢልዮን ብር ፣ አጠቃላይ ሀብት ከ 10.2 ቢሊዮን ብር በላይ ደርሷል ሲል አዋሽ ኢንሹራንስ ከላከልን መግለጫ ላይ ተመልክተናል፡፡
ንጋቱ ሙሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments