በአዲስ አበባ ከተማ የአየር ብክለት መጨመር ዋና ተጠያቂ ናቸው የተባሉ በካይ ጋዝ የሚለቁ መኪኖችን የተሽከርካሪዎቹ ባለቤቶች እንዲያስጠግኗቸው ሊገደዱ ነው፡፡
የማያስጠግኗቸው ከሆነ መኪኖቹ በከተማዋ እንዳይሽከረከሩ እግድ እንዲጣል የሚያስገድድ መመሪያ ስራ ላይ ሊውል መሆኑ ተሰምቷል።
መመሪያው በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ ተግባራዊ እንደሚደረግም ሰምተናል።
የካርበንና መሰል በካይ ልቀት መጠንን ለመቆጣጠር የሚከወነው ስራ ከአመታዊ የተሽከርካሪ ምርመራ ቁጥጥር (ቦሎ) ጋር ይካተታልም ተብሏል።
በዚህም የጋዝ ልቀት መጠናቸው ከመደበኛው በላይ አልፈው የተገኙ የተሽከርካሪዎች አመታዊ የቦሎ ዕድሳት እንደማይደረግላቸውም ተነግሯል።
አብዛኞቹ ተሽከርካሪዎች የጋዝ ልቀት መጠናቸው ከመደበኛው በላይ የሚያልፉት ከተሸከርካሪዎች አሮጌነት ብቻ የመጣም ሳይሆን በየጊዜው አስፈላጊውን ሰርቪስ በማይደረግባቸው አዳዲስ ተሽከርካሪዎች ላይም ችግሩ ይስተዋላል ተብሏል።
በአዲስ አበባ ከተማ ከሚከሰተው የአየር ብክለት ውስጥ 27 በመቶው ከተሽከርካሪዎች የጭስ እና የጋዝ ብናኝ ምክንያት የሚመጣ መሆኑንም የአዲስ አበባ ከተማ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ተናግሯል።
ፍቅሩ አምባቸው
Yorumlar