በኢትዮጵያ በማህበራዊ የትስስር ገፆች ላይ የሚተላለፍ የጥላቻ ንግግር እና የሀሰተኛ መረጃ መጠኑ ጨምሯል ተባለ።
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ይህንን ያለው፤ ዛሬ በማህበራዊ የትስስር ገጾች የጥላቻ ንግግር እና ሀሰተኛ መረጃ ሀገራዊ ሪፖርትን ይፋ ባደረገበት ወቅት ነው።
ጥናቱ የተካሄደው 5 የማህበራዊ ገፆችን ትኩረት አድርጎ መሆኑ የተነገረ ሲሆን ፌስቡክ፣ ዩቲዩብ፣ ኤክስ፣ ቴሌግራም እና ቲክቶክ ላይ ጥናቱ እንደተካሄደ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ሲናገር ሰምተናል።
በሪፖርቱም የጥላቻ እና ሀሰተኛ መረጃ ስርጭቱ ካለፈው አመት ጋር ሲነፃፀር ብሄር ተኮር እና የፖለቲካ ጉዳዮች ይበዙ እንደነበር የተናገው ባለስልጣኑ በ2016 ግማሽ አመት ከብሄር ጉዳዩች ይልቅ የፖለቲካ ሀሰተኛ መረጃ ስርጭቶች እንደጨመረ ጥናቱ ያሳያል ተብሏል።
በኤክስ ገፅ 66 በመቶ፣ በፌስቡክ 63 በመቶ፣ በቴሌግራም 59 በመቶው በፅሁፍ የተሰራጩ ሀሰተኛ መረጃዎች ሲሆኑ በምስል እና በፅሁፍ የተላለፉት ደግሞ በኤክስ 12 በመቶ እና በቴሌግራም 18 በመቶ መሆኑ ተነግሯል።

በቪዲዮ ከተላለፉ ሀሰተኛ መረጃዎች መካከል ደግሞ በቲክቶክ 74 በመቶ እና በዩቲዩብ 70 በመቶ ነው የተባለ ሲሆን በዚህ ምክንያትም ባለፉት ስድስት ወራት በቴሌግራም፣ በዩቲዩብ እና በቲክቶክ የትስስር ገፆች ላይ የሚሰራጩ የጥላቻ ንግግሮች ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳሉ መባሉን ሲነገር ሰምተናል።
ከዓመት በፊት በኢትዮጵያ የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ቁጥር 6.4 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን ከዚህ ውስጥ ደግሞ ፌስቡክ 90.71 ከመቶ፣ ዩቲዩብ 2.95 በመቶ እና የኤክስ ተጠቃሚ 1.8 በመቶ መሆኑን ተነግሯል።
የቲክቶክ እና የቴሌግራም ተጠቃሚዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ጥናቶች ያሳያሉ ሲል የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሀን ባለስልጣን አስረድቷል።
ፋሲካ ሙሉወርቅ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: @ShegerFMRadio102_1
Youtube: http://tiny.cc/ShegerFM1021Radio
Website: https://www.shegerfm.com/
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments