መጋቢት 12፣2016 - በትግራይ ክልል ያለው የምግብ እጥረት ካልተፈታ ከ223 ሺህ በላይ ተማሪዎች እስከ ዓመቱ መጨረሻ ወደ ተማሪ ቤት ላይሄዱ ይችላሉ ተባለ
- sheger1021fm
- Mar 21, 2024
- 1 min read
በትግራይ ክልል ያለው የምግብ እጥረት በሚቀጥሉት ወራት ካልተፈታ ከ 223 ሺህ በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች እስከ ዓመቱ መጨረሻ ወደ ተማሪ ቤት ላይሄዱ ይችላሉ ተባለ፡፡
የነበረው ጦርነት፣ ድርቅ፣ የምግብ እጥረት እና የትምህርት ቁሳቁስ አለመሟላት በትግራይ ክልል ያሉ ተማሪዎች አሁንም በሙሉ አቅማቸው ትምህርት እንዳይከታተሉ እንቅፋት እንደሆነ ተነግሯል፡፡
የትግራይ ክልል ትምህርት ቢሮ ሀላፊ ዶክተር ኪሮስ ጉዕሽ፤ 2 ጊዜ ተደረገ ባሉት ዳሰሳዊ ጥናት ተማሪዎች እየገጠማቸዉ ባለው የግብዓት እጥረት ምክንያት ትምህርታቸዉን ለመቀጠል እየተቸገሩ ነዉ፡፡
የትምህርት ቢሮው ሀላፊ በተለይም ተማሪዎች ምግብ ማጣታቸው ትምህርት እንዲያቋርጡ እያደረጋቸዉ ነው፤ በየካቲት ወር ብቻ 20 ሺህ ተማሪዎች በዚህ ምክንያት ትምህርታቸውን አቋርጠዋል ብለዋል፡፡
የምግብ እጥረቱ በሚቀጥሉት ወራቶች ካልተፈታ በክልሉ ከሁለት መቶ ሀያ ሶስት ሺህ በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች እስከ አመቱ መጨረሻ አይቀጥሉም ብለዋል፡፡
ክልሉ የአንደኛ ደረጃ ክፍል መፅሐፍ ህትመት አከናውኖ ለተማሪዎች ማድረስ የነበረበት ቢሆንም በቂ በጀት ስለሌለዉ ቢሮው መፅሐፍቶቹን አትሞ ለተማሪዎች ማከፋፈል አለመቻሉን ኃላፊዉ ይናገራሉ፡፡
ከክልሉ ህዝብ ውስጥ 30 በመቶዉ ተማሪ ነው ያሉ ሲሆን እረጂ ተቋማት እና የፌደራል መንግስት እርዳታቸው ሲሰጡ ይህንን ያማከለ ሊሆን ይገባል ሲሉ ዶክተር ኪሮስ አሳስበዋል፡፡
አሁን ላይ ከፌደራል መንግስት የተለየ የበጀት ድጋፍ ለትምህርቱ ዘርፍ እየተደረገለት አይደለም፣ ችግሩ ጊዜ የሚሠጠዉ ባለመሆኑ አፋጣኝ ድጋፎች ያስፈልጋል በማለት ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
በረከት አካሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Website: https://www.shegerfm.com/
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments