መጋቢት 11 2017 - እናት ባንክ የድካማቸውን ያህል ያልተነገረላቸውን ብዙሃን ኢትዮጵያን እናቶችን የሚወክል "እማዬ" የተሰኘ ቅርንጫፍ ከፈተ።
- sheger1021fm
- Mar 20
- 1 min read
እማዬ የተሰኘው አዲሱ ቅርንጫፍ ልጆች ለእናቶቻቸው ፕሮግራሞችን በነፃ ማዘጋጀት የሚችሉበት መሆኑም ተነግሯል።
ይህ በአይነቱ የተለየ ነው የተባለለት አዲሱ ቅርንጫፍ ከባንክ አገልግሎቱ በተጨማሪ ተጓዳኝ የሆኑ ተግባራት ይከውንበታል ተብሏል።
ባንኩ "እማዬ" የሚል ስያሜ የሰጠው ይህ ቅርንጫፍ በእናትነታቸው ብዙ ዋጋ የከፈሉ ነገር ግን የልፋታቸውን ያህል ያልተነገረላቸው እናቶች ውክልና እንዲኖራቸው ታስቦ የተከፈተ ነው የተባለ ሲሆን እናት ባንክ ዛሬ የከፈተውን ቅርንጫፉን ጨምሮ የቅርንጫፎቹ ብዛት 207 መድረሳቸውን ተናግሯል።
በተጨማሪም በእናቶች ላይ ጥናት እና ምርምር ማድረግ ለሚፈልጉ ሁሉ በቅርንጫፉ የሚሰሩበት ቦታም የተዘጋጀ መሆኑ የተነገረ ሲሆን ልጆች ለእናቶች ልዩ ልዩ ፕሮግራሞችን በነፃ ማዘጋጀት የሚችሉበት ነው።
በሌላ በኩል ባንኩ ያዘጋጀው "ለእናቴ" እና "የአመቱ ድንቅ እናት" የፅሁፍ ውድድር ጥር 30 ቀን 2017 ዓ.ም መጠናቀቁ ቢታወቅም አዲሱን "እማዬ" የተሰኘውን ቅርንጫፍ መክፈትን በምክንያት በማድረግ ለአስር ቀናት ማራዘሙን ተናግሯል።

በዚህም በአዲስ አበባ የምትገኙ እና በውድድሩ መሳተፍ ለሚፈልጉ በአዲሱ ቅርንጫፍ እንዲሁም በክልሎች ላላችሁ ተወዳዳሪዎች ስራዎቻቸውን በአካባቢያቸው በሚገኝ ቅርንጫፍ ማስገባት ትችላላችሁ ተብላችኋል።
እማዬ የተሰኘው ቅርንጫፍ ፒያሳ አቡነ ጴጥሮስ መታሰቢያ ሃውልት ትይዩ በሚገኘው የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጋዜጠኝነት እና የኮሙኒኬሽን ትምህርት ቤት አዲስ ህንፃ ላይ ይገኛል።
ፋሲካ ሙሉወርቅ
Comments