መስከረም 9 2018 - ግንባታው ሲጀመር ከተያዘለት ወጪ ተጨማሪ 90 ሚሊዮን ዶላር የጠየቀው የሞጆ ደረቅ ወደብ ማስፋፊያ ፕሮጀክት፤ በቅርቡ ይመረቃል
- sheger1021fm
- Sep 19
- 1 min read
ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ይሰጣል የተባለው የሞጆ ደረቅ ወደብ ማስፋፊያ ፕሮጀክት በሁለት ወራት ውስጥ እንደሚመረቅ የተናገረው የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር ነው፡፡
የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ድኤታ ደንጌ ቦሩ ፕሮጀክቱ ከ240 ሚሊዮን ዶላር (በአሁኑ የምንዛሪ ተመን 38 ቢሊዮን ብር) በላይ ወጪ እንደተደረገበትና በሁለት ወራት ውስጥም እንደሚመረቅ ጠቅሰዋል፡፡
ከ6 ዓመት በፊት የሞጆ ደረቅ ወደብ ማስፋፊያ ፕሮጀክት በተጀመረበት ወቅት፤ የግንባታው ወጪ በ150 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንደነበረ መነገሩ ይታወሳል፡፡
በ2011 ዓ.ም ተጀምሮ ይጠናቀቃል ተብሎ ከተያዘለት ጊዜ 3 ዓመታትን የተሻገረው ፕሮጀክቱ ሲጀመር ከተያዘለት ወጪ ተጨማሪ 90 ሚሊዮን ዶላር መጠየቁ ተሰምቷል፡፡

የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ድኤታ ደንጌ ቦሩ ኢትዮጵያ እያከናወነቻቸው ካሉ ትላልቅ ፕሮጀክቶች የሞጆ ደረቅ ወደብ ማስፋፊያ አንደኛው እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
ሀገር ማደግ የምትችለው የሎጀስቲክስ ስርዓቷ ቀልጣፋ ሲሆን ነው ያሉት ሀላፊው፤ የሎጀስቲክስ ስርዓት ቀልጣፋ ካልሆነ የምንፈልገው እድገት ማምጣት አንችልም ብለዋል፡፡
ሚኒስትር ድኤታው ይህንን የተናገሩት፤ ስለ ሀገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፉ እድገትና አሁን ያለበት ደረጃ፤ ከሰሞኑ በተለያዩ ዘርፍ ላሉ ባለሞያዎች ማብራሪያ በሰጡበት መድረክ ላይ ነው፡፡
ፕሮጀክቱ ይጠናቀቃል ተብሎ ከተያዘለት ጊዜ መዘግየቱ ከወራት በፊት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ጭምር ጥያቄ ተነስቶበት፤ የሲሚንቶ እጥረት ግንባታው እንዲጓተት ካደረጉት ምክንያቶች ቀዳሚ መሆኑንም ተነግሮ ነበረ፡፡
ማንያዘዋል ጌታሁን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments