ዛሬ ከረፉዱ 3 ሰዓት ሳሪስ አደይ አበባ ከሚገኘው የመኖሪያ ቤታቸው ወደ ሚሊኒየም አዳራሽ አሸኛኘት ተደርጓል።
ከዚያም በሚሊኒየም አዳራሽ የተለያዩ የሽኝት ፕሮግራሞች የተካሄዱ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ሀላፊዎች ተገኝተዋል።
የቀብር ስርዓታቸውም ከቀኑ 8:00 ሰዓት በአዲስ አበባ በጴጥሮስ ወጳውሎስ መካነ መቃብር ተፈፅሟል።
በቀብር ስርዓቱ ላይም ቤተሰቦቻቸው፣ የስራ ባልደረቦቻቸው ተገኝተዋል።
ፖለቲከኛው እና መምህሩ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ከትናንት በስቲያ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ይታወሳል።

አብዛኛውን የህይወት ዘመናቸውን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በማስተማር ያሳለፉት ፕሮፌሰር በየነ በፓለቲካ ተሳትፏቸው በሰላማዊ ትግል አራማጅነታቸው ይታወሳሉ።
ፕሮፌሰር በየነ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሆነው ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡
የመድረክ እንዲሁም ኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ(ኢሶዴፓ) ሊቀመንበርም ነበሩ፡፡
በ75 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ፕሮፌሰር የሁለት ወንድ እና የሁለት ሴት ልጆች አባት ናቸው።
ሸገር በፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ህልፈት የተሰማውን ሀዘን እየገለፀ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መፅናናትን ይመኛል።
ንጋቱ ሙሉ
Comments