መስከረም 8 2018 - የስራ ክህሎት እና የፈጠራ ሀሳብ ያላቸው ነዋሪዎችን ለማሰልጠን ከ4,000 በላይ አሰልጣኞች ተሰማርተዋል ተባለ
- sheger1021fm
- Sep 18
- 1 min read
በየመንደሩ ቀጭቃጭ፣ ሸክላ ሰሪ እና ሌላም ሌላ እየተባሉ ቦታ የማይሰጣቸውና መሰል የተለያየ የስራ ክህሎት እና የፈጠራ ሀሳብ ያላቸው ነዋሪዎችን ለማሰልጠን ከ4,000 በላይ አሰልጣኞች ተሰማርተዋል ተባለ፡፡
ይህም ሀገር በቀል የስራ ፈጠራዎች እና የጎጆ ኢንዱስትሪዎችን የተሻለ ውጤታማ ለማድረግ እንደሚረዳ ተነግሯል፡፡
ይህንን የነገሩን በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የኢኖቬሽን እና ኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኃላፊ የሆኑት ብርሃኑ አደሬ ናቸው፡፡
እነዚህ አሰልጣኞች እንዴት ነው ስራቸውን የሚከውኑት ብለን ለሀላፊው ላነሳነው ጥያቄ፤ አሰልጣኞቹ በተለያየ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚገኙ ነባር የስራ ባህሎችን በመለየት ህብረተሰቡን በማወያየት እና ከነባሩ በተሻለ መልኩ አድጎ የገቢ ምንጭ እንዲሆኑ ሞያዊ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡

የተለያዩ የማህበረሰቡ ክፍሎች የተለመዱ የስራ ባህልምና የሰው ሀብት እንዳለ የሚጠቅሱት ሀላፊው እነዚህን ሀብቶች በማዘመን እና ሳይንሳዊ በመሆኑ መንገዶች ማገዝ ያስፈልጋልም ብለዋል፡፡
እያንዳንዱ መንደር እና አካባቢ የሚታወቅበት የስራ ባህል ተለይቶ ማህበረሰቡ በለመደው የስራ ሁኔታን በማበርታት ቢያንስ በአንድ መንደር አንድ የዳበረ እና ከነባሩ የተሻለ ጠቃሚ የጎጆ ኢንዱስትሪም ሆነ ውጤት የሚያስገኝ ስራ እንዲሰራ ነው እየጣርን ያለነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
እንደ ሀገር የጎጆ ኢንዱስትሪ ዉስጥ የሚሰሩ ስራዎች ብዙ ቢሆንም በማሳደጉ ከሌሎች ሀገራት ሲተያይ ወደኋላ የቀረ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ይህም የሆነው በዘርፉ ያሉ ችግሮች ስላሉ ነው፤ ችግሮቹን ለመፍታት ብዙ ስራዎች ከመንግስት ይጠበቃል፤ በዚህ ረገድ እነዚህ ከ4,000 በላይ አሰልጣኞች ወደ ማህበረሰቦች ተሰማርተው አስተዋጽኦ እያደረጉ እንደሆነም አቶ ብርሀኑ አደሬ ያብራራሉ፡፡
በየቦታው የስራ እና የፈጠራ ክህሎት ያላቸው ሰዎችን በመደገፉ ስራና ክህሎት ሚኒስቴር ብቻውን ሊተውለት የሚገባ ጉዳይ ሳይሆን ሌሎች የፋይናን እና የሚመለከታቸው ተቋማት ድጋፍ እንደሚስፈልጋቸውም አንስተዋል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ…..
ማንያዘዋል ጌታሁን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments