መስከረም 22፣2017 - ኢዜማ ‘’ህዝባዊ በዓላትን ለየትኛውን ዓይነት የፖለቲካ አጀንዳ ማራመጃነት መጠቀም ተገቢ አይደለም’’ አለ
- sheger1021fm
- Oct 2, 2024
- 1 min read
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ(ኢዜማ) ‘’ህዝባዊ በዓላትን ለየትኛውን ዓይነት የፖለቲካ አጀንዳ ማራመጃነት መጠቀም ተገቢ አይደለም’’ አለ፡፡
ፓርቲው ለሸገር በላከው መግለጫ የጋራ ማንትን በመፍጠር ሚናቸው ከፍተኛ የሆኑ ባህሎችን በእኩል መንከባከብ እና ማሳደግ ተገቢ ነው ብሏል፡፡
ይሁንና መሰል ባህሎችን እና በዓላትን የጋራ ማንነት ማጠንከሪያ ምሶሶ ከማድረግ ይልቅ የፖለቲካ ውግንና ማሳያ ሲሆኑ ታዝቢያለሁ ብሏል ፓርቲው፡፡
‘’በደማቅ ሁኔታ ሊከበሩ ከሚገቡ ባህሎች መካከል ነው’’ ያለውን የኢሬቻ በዓልን በተመለከተም መንግስት ካለበት ሀላፊነት እላፊ ጣልቃ ገብቷል ባይ ነው ኢዜማ፡፡

በመንግስታዊ ሀላፊነት ቦታ ላይ የተቀመጡ ባለስልጣናትን ጨምሮ ከህዝባዊ ባህል እሴቱ ባፈነገጠ መንገድ ፖለቲከኞቹ ዋነኛ አጋፋሪ ሆነዋል ብሏል፡፡
‘’አካሄዱ በሌሎች ላይ ስጋት እና የመገለል ስሜትን ይፈጥራል’’ ያለው ኢዜማ በተለይ በመንግስት ተቋማት በሚፃፉ ደብዳቤ ከተቋማት እና ከንግዱ ማህበረሰብ ከአቅም በላይና አስገዳጅ ከፍተኛ የገንዘብ መዋጮ መጠየቁንም በመጥቀስ ትክክል አይደለም ብሏል፡፡
እንዲህ ያለው ነገርም ባህሉን በምሬት እና በስጋት እንዲመለከቱትም ያደርጋል ሲል ስጋቱን በመግለጫው ጠቅሷል፡፡
በመሆኑም በንግዱ ማህበረሰብ ላይ እየተደረገ ያለው ተጠያቂነት የሌለበት ህገ-ወጥ ጫና እንዲቆም ኢዜማ ጠይቋል፡፡
‘’ሀይማኖታዊ በዓላትን ለፖለቲካ ፍጆታ ማዋልም ባህሉን መበረዝ ነው’’ ሲል በመግለጫው አክሏል፡፡
Comentários