መስከረም 22፣2017 - ተደጋጋሚ የአእምሮና የስነ ልቦና ቁስለት እንዴት ይታከም ይሆን?
- sheger1021fm
- Oct 2, 2024
- 2 min read
በጦርነት የሚመጣ ተደራራቢ የአእምሮ ቁስለት በባለሞያዎቹ አጠራር(Psychological Trauma) እንዴት ይታከም ይሆን?
በሰሜኑ ጦርነት ሰለባ የነበሩ በጦርነቱ ቀጠና ያሉ ሰዎች ለደረሰባቸው ከባድ የአእምሮ ቁስል ምንም እንኳን አጥጋቢ ባይሆንም በስነ ልቦና ባለሞያዎች ጠባሳቸው እንዲሽር የማድረግ ስራ ተሰርቷል ተብሏል፡፡
አጋር ከሚላቸው የስነ ልቦና ባለሙያዎች ጋር በመሆን ይህንን ስራ መከወኑን የተናገረው የአሜሪካ መንግስት የልማት ተራዕዶ ድርጅት(USAID) ነው፡፡
ከጦርነቱ በኋላ በጥቂቱም ቢሆን ፋታ አግኝተዋል፣ ታክመዋል የተባሉት በአማራ ክልል ያሉ ነዋሪዎች ለዳግም የአእምሮ ቁስለት ተዳርገዋል፡፡
እንዲህ ያለው ተደጋጋሚ የአእምሮና የስነ ልቦና ቁስለት እንዴት ይታከም ይሆን?
በጦርነቱ ቀጠና ያሉ ሰለባዎችን የአእምሮ ቁስለት ሲያክሙ የነበሩ የስነ ልቦና ባለሙያዋን ትዕግስት ዋልተ ንጉስን ጠይቀናል፡፡
እንዲህ ዓይነቱ በጦርነት ምክንያት የሚመጣ የአእምሮ ቁስለት ከግለሰቡ አልፎ ወደ ቀጣዩ ትውልድ የሚሸጋገር መሆኑን አለም ላይ የተደረጉ ጥናቶች እንዳሳዩትና በኢትዮጵያ ያለው የከፋ መሆኑን ባለሙያዋ ይናገራሉ፤ ችግሩ ከኢኮኖሚውና ከሌላውም እኩል ሊታሰብበት ይገባል ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ተባብሰው የቀጠሉት ግጭቶች አንድ ቦታ እንዲያበቁ ካልተደረገ የኢትዮጵያ ነገ ያስፈራኛል፤ሃገር ተረክቦ የሚያስቀጥል ትውልድ እንዳናጣ እፈራለሁ ይላሉ ባለሙያዋ፡፡
በጦርነትና ግጭቶች ውስጥና በዙሪያ ያሉ ሰዎች ጦርነቱ በሚያስከትለው ጉዳት የመጀመሪያ ተጠቂዎች ቢሆኑም እንደ አዲስ አበባ ራቅ ብለው ያሉ ሰዎችም ደረጃው ቢለያይም የአእምሮ ጠባሳው ተጠቂዎች ሆነዋል የሚሉት የስነ ልቦና ባለሙያዋ ትዕግስት ዋልተንጉስ ኢትዮጵያ እንድታገግም ካስፈለገ ይህም መታከም እንዳለበት ያነሳሉ፡፡
እንደ ሃገር ለመታከም በራሳችሁ ከመጣር ባለፈ ይመለከታቸዋል ከሚባሉት ጋር ተቀራርባችሁ ለመስራት ምን አድርጋችዋል? ላልናቸው ሲመልሱ የቆይታ ጊዜውን አጠናቅቋል በሚል ከፈረሰው የእርቀ ሰላም ኮሚሽን ጋር በዚህ ጉዳይ ላይ አብረን ለመስራት እየተነጋገርን ነበር ግን ወደ ተግባር ሳንገባ ኮሚሽኑ የስራ ጊዜውን አጠናቅቋል ተብሎ ስለፈረሰ መስራት አልቻልንም ብለዋል፡፡
የሰሜኑ ጦርነት ሰለባዎችን በስነ ልቦና ለማከም የአሜሪካ መንግስት የልማት ተራድኦ ድርጅት ዩኤስ አይዲ ባደረገው ድጋፍ በሁለቱ ክልሎች ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎችን መድረስ ተችሏል፡፡
ይሁንና ይህንን መሰሉን የአእምሮን ቁስለት ለማከም ለአጭር ጊዜ የሚከወኑ ፕሮጀክቶች ሳይሆኑ እንደ ችግሩ መክፋት ለኤች አይቪ እና ለኮቪድ የተሰጠው ዓይነት ሰፋ ያለ መንግስታዊ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ባለሙያዋ ተናግረዋል፡፡
ሙሉ ዘገባውን በድምፅ ለማድመጥ...
ምንታምር ፀጋው
Comments