ሐምሌ 3፣ 2016 - ኢትዮ ቴሌኮም ከተጀመረ 3 ዓመት በሞላው ቴሌብር የተገላበጠው ገንዘብ፤ 2.55 ትሪሊየን ብረ ነው አለ
- sheger1021fm
- Jul 10, 2024
- 1 min read
በተጠናቀቀው 2016 በጀት ዓመትም ኩባንያው የተጣራ 21.79 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ተሰምቷል።
ትርፉ ከእቅዱ አኳያ ሲታይ 108.7 በመቶ ነው ተብሏል።
ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ሲነፃፀር 20.9 በመቶ እድገት ተመዝግቧል።
ይህ የተሳካው በብዙ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ መሆኑን የኩባንያው ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ተናግረዋል።
ኩባንያው በበጀት ዓመቱ አጠቃላይ 93.7 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱንም ተናግሯል።
ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲመሳከር የ21.7 በመቶ እድገት አሳይቷል።
ገቢው የእቅዱን 103.6 በመቶ መሆኑን ዋና ስራ አስፈፃሚዋ የኩባንያውን 2016 በጀት ዓመት የስራ አፈፃፀም ለጋዜጠኞች ሲናገሩ ሰምተናል።
ኩባንያው 29.76 ቢሊዮን ብር ታክስ ከፍሏል ተብሏል።
9.97 ቢሊን ብር ደግሞ የትርፍ ድርሻ ክፍፍል መፈፀሙን አስረድቷል።
2016 የበጀት ዓመትን በላቀ ስኬት ማጠናቀቁን የተገረው ኢትዮቴሌኮም የደንበኞቹ ብዛት 78.3 ሚሊዮን መድረሱንም ተናግሯል።
የቴሌብር ደንበኞች ቁጥርም 47.55 ሚሊየን ደርሷል።

በቴሌ ብር ብድር ያገኙ ደንበኞች ቁጥር 5.3 ሚሊየን ተመዝግቧል።
በዘንድሮ የስራ ዘመን ለ 2.92 ሚሊየን ደንበኞች 9.57 ቢሊየን ብር ብድር መሰጠቱን ፍሬህይወት ታምሩ ተናግረዋል።
ከኢትዮጵያ ህዝብ 99.2 በመቶ፣ ከአገሪቱ አካባቢ 85.4 በመቶ የቴሌኮም አገልግሎት እንዲያገኙ ማድረጉን ዋና ስራ አስፈፃሚዋ ሲናገሩ ሰምተናል።
ኩባንያው የአገልግሎት ቅናሽ በማድረግ ከአፍሪካ በድምፅ አንደኛ፣ በዳታ ሁለተኛ መሆኑን አለም አቀፍ አጥኚዎች እንደመሰከሩለት ተሰምቷል።
ዘንድሮ ኩባንያው የውጭ ምንዛሪ እጥረት፣ የፋይበር መቆራረጥ፣ የመሰረተ ልማት መሰበር፣ መዘረፍና መሰረቅ፣ የእቃ አቅርቦት ችግር፣ ለሞባይል ጣቢያ ግንባታም የመሬት አቅርቦት ችግር እንደገጠመው ተናግሯል።
ለመሰረተ ልማት ግንባታና ሞባይል ጣቢያ ለመትከል የደንበኞችንም ቅሬታ ለመመለስ በአዲስ አበባና ሌሎች ከተሞች የመሬት አቅርቦት ችግር ማጋጠሙም ተሰምቷል።
ተህቦ ንጉሴ
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Comments