ሐምሌ 23፣2016 - ሁሉም የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ዳግም እንዲመዘገቡ ተወሰነ
- sheger1021fm
- Jul 30, 2024
- 1 min read
ሁሉም የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ዳግም እንዲመዘገቡ ተወሰነ፡፡
እስከ መጪው ታህሳስ ወር መጨረሻ ዳግም ምዝገባው ካላደረጉ ይሰረዛሉም ተብሏል፡፡
ይህ የተባለው የትምህርትና ስልጠና ባለሥልጣን እና ትምህርት ሚኒስቴር፤ የግል ኮሌጆች ዳግም ምዝገባን አስመልክቶ ከሚመለከታቸው ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት ነው።
በተሻሻለው መመሪያ መሰረት የትምህርት ተቋማቱ የዳግም ምዝገባ ማድረግ እንደሚገባቸው የትምህርት ሚኒስትሩ ብርሃኑ ነጋ(ፕ/ር) ተናግረዋል።

ትምህርት ሚኒስቴር፤ የሁሉም የመንግስት እና የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መረጃ የሚመዘገብበት የመረጃ ቋት(HEMIS) መዘጋጀቱን ተነግሯል፡፡
በዚህም ሁሉም ተቋማት ሙሉ መረጃቸውን በሲስተሙ ላይ የማስመዝገብ ግዴታ አለባቸው ተብሏል።
ተቋማቱ ከዚህ ቀደም ጀምሮ እንደመዘገቡ ቢነገራቸውም ከ382 የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ እስካሁን የተመዘገቡት 83ቱ ብቻ እንደሆኑ ተነግሯል፡፡
በትምህርትና ስልጠና ባለሥልጣን የከፍተኛ ትምህርት ፍቃድ አሰጣጥ መሪ ስራ አስፈጻሚ ህይወት አሰፋ፤ በከፍተኛ ትምህርት እና የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ተቋማት የፈቃድ እና ፈቃድ ዕድሳት አሰጣጥ መመሪያ፣ ስታንዳርዶች እና የዳግም ምዝገባ መምሪያ ዙሪያ ለተሳታፊዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በሌላ በኩል ዘንድሮ በተሰጠው የመውጫ ፈተና 22 የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አንድም ተማሪ አላሳለፋም ተብሏል፡፡
202 የግል የከፍተኛ ተቋማት በ2016 ዓ.ም የመውጫ ፈተና ያስፈተኑ ቢሆንም ካስፈተኗቸው ተማሪዎች መካከል ያሳለፋት 13 በመቶ ብቻ እንደሆነ ተነግሯል።
ከ202ቶቹ መካከልም ከ25 በመቶ በላይ ያሳለፉት በቁጥር 29ኙ ብቻ ናቸው ተብሏል፡፡
የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ አጠቃላይ ካስፈተኗቸው ተማሪዎች 58 በመቶ አሳልፈዋል ተብሏል።
ማንያዘዋል ጌታሁን
Comments