top of page

ሐምሌ 10፣2016 - በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ ፈቃድ መስጠት የሚያስችል መመሪያ በካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ወደ ስራ እንዲገባ ተደረገ

በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ ፈቃድ መስጠት የሚያስችል መመሪያ በካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ወደ ስራ እንዲገባ ተደረገ።


"የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች፤ የተዛማጅ ውሎች እና ያልተማከለ የጠረጴዛ ዙሪያ ገበያዎች የፈቃድ አሰጣጥ፣ የአሰራር እና የቁጥጥር መመሪያ ቁጥር 1009/2016 ከሐምሌ 9 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ስራ ላይ ውሏል ሲል የካፒታል ገበያ ባለስልጣን ተናግሯል ፡፡


መመሪያው በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያን እና ያልተማከለ የጠረጴዛ ዙሪያ ገበያን ፈቃድ ለመስጠት የሚያስችል ሲሆን የመንግስት እና የግል ድርጅቶች ገበያውን በመጠቀም የድርጅቶችን የድርሻ እና የብድር ሰነዶችን በመሽጥ እና ገንዘብ በመስብሰብ ፕሮጀክቶችን ለመስራት አቅም ለመፍጠር ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ተብሎለታል፡፡


በሌላ በኩል መመሪያው መውጣቱ የድርሻ ወይም የብድር ሰነድ መግዛት የሚፈልግ ማንኛውም ሰው ወይም ኢንቨስተር ፈቃድ ካለው ገበያ አስፈላጊው ቁጥጥርና ግልጸኝነት በተሟላበት የግብይት አሰራር፣ ፈቃድ ባለው ተገበያይ አማካኝነት የተፈቀዱ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮችን ለመግዛት እና ለመሸጥ ምቹ ሁኔታ ይፈጥረለታል ሲል ባለስልጣን መ/ቤቱ አስረድቷል፡፡


ይህም በተበታተነ መልኩ የሚደረገውን የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ግብይት ወደ አንድ ፈቃድ ወደሚሰጠው እና ቁጥጥር ወደሚደረግበት ሰነደ መዓለ ንዋዮች ገበያ በማምጣት ዘርፉ ለተዋናዮቹ እና ለሀገር ኢኮኖሚ ከፍተኛ  አስተዋጽዖ  ያበረክታል ተብሎለታል፡፡


መመሪያው በመቋቋም ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ የስነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ  በመመሪያው መሠረት አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታዎች ሲያሟላ ፈቃድ በመስጠት ሥራ ለማስጀመር የሚያስችል ነው።


ንጋቱ ሙሉ

コメント


bottom of page