top of page

ህዳር 8፣2016 - አቢሲኒያ ባንክ በ2015 የበጀት ዓመት 5.23 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ ማግኘቱን ተናገረ።

አቢሲኒያ ባንክ በ2015 የበጀት ዓመት 5.23 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ ማግኘቱን ተናገረ።


ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀርም ትርፉ የ12.36 በመቶ ጭማሬ አለው ብሏል።


ባንኩ ይህንን ያለው 27ኛውን የባላክሲዮኖች ዓመታዊ የመደበኛ እና አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤውን ዛሬ ባካሄደበት ወቅት ነው።


በበጀት ዓመቱ ጠቅላላ ገቢው 22.73 ቢሊዮን ብር ነው የተባለ ሲሆን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር 6 ቢሊዮን ብር ወይም የ35.94 በመቶ እድገት አሳይቷል ተብሏል።


ከፍተኛውን ድርሻ የያዘው ከብድር ወለድ የተገኘው ገቢ መሆኑን ሲነገር ሰምተናል።


ባንኩ በበጀት ዓመቱ 17.5 ቢሊዮን ብር ማውጣቱን የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ መኮንን ማንያዘዋል ተናግረዋል።


ይህም ከባለፈው ዓመት የወጭ መጠን ጋር ሲነፃፀር 5.44 ሚሊዮን ብር ወይም በ45.10 በመቶ እድገት መሆኑን ተናግረዋል።


የአቢሲኒያ ባንክ አጠቃላይ ሀብቱን 189.51 ቢሊዮን ብር ደርሷል ያሉት አቶ መኮንን ማንያዘዋል ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር 40.06 ቢሊዮን ብር ወይም የ26.81 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን ተናግረዋል።


በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት የባንኩ አጠቃላይ ካፒታል ወደ 19.47 ቢሊዮን ብር ከፍ እንዳለ የተናገሩት አቶ መኮንን የባንኩ የተከፈለ ካፒታል ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ከተመዘገበው 8.32 ቢሊዮን ብር ወደ 11.9 ቢሊዮን ብር መጨመሩን አስረድተዋል። ይህም የ43.02 በመቶ ጭማሬ ማሳየት ችሏል ተብሏል።


ባንኩ በሂሳብ ዓመቱ ከሰጠው ብድር የወጭ ንግድ፣ ኢንዱስትሪ እና የሀገር ውስጥ ንግድ 64.1 በመቶውን በመያዝ ከፍተኛውን ድርሻ ይይዛል የተባለ ሲሆን ለኢንዱስትሪ፣ ግንባታ እና ግብርና ዘርፎች ባንኩ የሰጠው ብድር ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር 18.94 ቢሊዮን ብር ጭማሪ አሳይቷል ሲባል ሰምተናል።


አቢሲኒያ ባንክ በተጠናቀቀው የሂሳብ ዓመት 123 አዳዲስ ቅርንጫፎችን ከፍቷል የተባለ ሲሆን አጠቃላይ ባንኩ ቅርንጫፎቹም 864 ደርሰዋል ተብሏል።



ፋሲካ ሙሉወርቅ



የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ… https://bit.ly/33KMCqz

bottom of page